unfoldingWord 44 - ጴጥሮስና ዮሐንስ ይለምን የነበረውን ሰው ፈወሱ
概要: Acts 3-4:22
文本編號: 1244
語言: Amharic
聽眾: General
類型/流派: Bible Stories & Teac
目的: Evangelism; Teaching
聖經摘錄: Paraphrase
狀態: Approved
腳本是翻譯和錄製成其他語言的基本指南,它們需要根據實際需要而進行調整以適合不同的文化和語言。某些使用術語和概念可能需要有更多的解釋,甚至要完全更換或省略。
文本文字
አንድ ቀን ጴጥሮስና ዮሐንስ ወደ ቤተ መቅደስ ይሄዱ ነበር። ወደ ቤተ መቅደሱ ደጃፍ እንደ ቀረቡ፣ ገንዘብ ይለምን የነበረ ሽባ ሰው ዐዩ።
ጴጥሮስ ሽባውን ተመለከተውና፣ “የምሰጥህ ምንም ገንዘብ የለኝም። ያለኝን ግን እሰጥሃለሁ። በኢየሱስ ስም ተነሣና ተመላለስ!” አለው።
ወዲያውኑ እግዚአብሔር ሽባውን ሰው ፈወሰው፣ እርሱም መራመድና መዝለል፣ እግዚአብሔርንም ማመስገን ጀመረ። በቤተ መቅደሱ አጥር ግቢ የነበሩት ሰዎች ተደነቁ።
ሕዝብም የተፈወሰውን ሰው ለማየት ፈጥነው ተሰበሰቡ። ጴጥሮስ እንዲህ አላቸው፣ “ይህ ሰው ስለ ተፈወሰ ለምን ተደነቃችሁ? በገዛ ኃይላችን ወይም በጎነታችን አልፈወስነውም። ይልቁንም ይህንን ሰው የፈወሰው የኢየሱስ ኃይልና ኢየሱስ የሚሰጠው እምነት ነው።”
“ኢየሱስን እንዲገድለው ለሮማው ገዥ የነገራችሁት እናንተ ናችሁ። የሕይወትን ጀማሪ ገደላችሁት፣ እግዚአብሔር ግን ከሙታን አስነሣው። ታደርጉት የነበረው ነገር ባይገባችሁም እንኳ፣ መሲሑ መከራ እንደሚቀበልና እንደሚሞት የተነገሩትን ትንቢቶች ለመፈጸም እግዚአብሔር በድርጊቶቻችሁ ተጠቀመ። ስለዚህ ኃጢአታችሁ ይታጠብላችሁ ዘንድ አሁን ንስሐ ግቡና ወደ እግዚአብሔር ተመለሱ።”
የቤተ መቅደሱ መሪዎች ጴጥሮስና ዮሐንስ ይናገሩት በነበረው ነገር በጣም ተበሳጩ። ስለዚህ ያዙአቸውና እስር ቤት አስገቡአቸው። ነገር ግን ብዙ ሰዎች የጴጥሮስን መልእክት አመኑ፣ በኢየሱስ ያመኑት ሰዎች ቊጥርም ወደ 5,000 ገደማ ዐደገ።
በማግስቱ፣ የአይሁድ መሪዎች ጴጥሮስንና ዮሐንስን ወደ ሊቀ ካህናቱና ወደ ሌሎቹ የሃይማኖት መሪዎች አመጡአቸው። ጴጥሮስንና ዮሐንስን፣ “ይህንን ሽባ ሰው በምን ኃይል ፈወሳችሁት?” ብለው ጠየቁአቸው።
ጴጥሮስ እንዲህ ብሎ መለሰላቸው፣ “ይህ ሰው በመሲሑ በኢየሱስ ኃይል ተፈውሶ በፊታችሁ ቆሞአል። እናንተ ኢየሱስን ሰቀላችሁት፣ እግዚአብሔር ግን እንደ ገና አስነሣው! እናንተ አልተቀበላችሁትም፣ ነገር ግን በኢየሱስ ኃይል ካልሆነ በቀር ሌላ የመዳን መንገድ የለም!”
ጴጥሮስና ዮሐንስ በጣም በድፍረት በመናገራቸው እነዚህ መሪዎች ደነገጡ፣ ምክንያቱም እነዚህ ሰዎች ያልተማሩ ተራ ሰዎች መሆናቸውን ማየት ችለው ነበር። ነገር ግን በዚያን ጊዜ እነዚህ ሰዎች ከኢየሱስ ጋር እንደ ነበሩ አስታወሱ። ጴጥሮስንና ዮሐንስን ካስፈራሩአቸው በኋላ፣ እንዲሄዱ ለቀቁአቸው።