unfoldingWord 45 - ፊልጶስና ኢትዮጵያዊው ባለ ሥልጣን
Контур: Acts 6-8
Сценарий нөмірі: 1245
Тіл: Amharic
Аудитория: General
Мақсат: Evangelism; Teaching
Features: Bible Stories; Paraphrase Scripture
Күй: Approved
Сценарийлер басқа тілдерге аудару және жазу үшін негізгі нұсқаулар болып табылады. Оларды әр түрлі мәдениет пен тілге түсінікті және сәйкес ету үшін қажетінше бейімдеу керек. Пайдаланылған кейбір терминдер мен ұғымдар көбірек түсіндіруді қажет етуі немесе тіпті ауыстырылуы немесе толығымен алынып тасталуы мүмкін.
Сценарий мәтіні
በጥንትዋ ቤተ ክርስቲያን ከነበሩት መሪዎች አንዱ እስጢፋኖስ ተብሎ የሚጠራ ሰው ነበር። እርሱ መልካም ስም ያለውና መንፈስ ቅዱስና ጥበብ የሞላበት ሰው ነበር። እስጢፋኖስ ብዙ ተአምራትን ያደረገና ሰዎች በኢየሱስ እንዲያምኑ አሳማኝ ምክንያት የሚያቀርብ ሰው ነበር።
አንድ ቀን እስጢፋኖስ ስለ ኢየሱስ በሚያስተምርበት ጊዜ፣ በኢየሱስ ያላመኑ አንዳንድ አይሁድ ከእስጢፋኖስ ጋር መከራከር ጀመሩ። በጣም ተቈጡና ስለ እስጢፋኖስ ለሃይማኖት መሪዎች ዋሽተው ተናገሩ። “ስለ ሙሴና ስለ እግዚአብሔር ክፉ ነገሮችን ሲናገር ሰምተነዋል!” አሉ። ስለዚህ የሃይማኖት መሪዎቹ እስጢፋኖስን ያዙትና ተጨማሪ የሐሰት ምስክሮች ስለ እስጢፋኖስ ዋሽተው ወደተናገሩበት ወደ ሊቀ ካህናቱና ወደ ሌሎቹ የአይሁድ መሪዎች አመጡት።
ሊቀ ካህናቱ እስጢፋኖስን፣ “እነዚህ ነገሮች እውነት ናቸውን?” ብሎ ጠየቀው። እስጢፋኖስ ከአብርሃም ዘመን ጀምሮ እስከ ኢየሱስ ዘመን ድረስ እግዚአብሔር ስላደረጋቸው ብዙ ታላላቅ ነገሮች፣ እንዲሁም የእግዚአብሔር ሕዝብ በተከታታይ በእርሱ ላይ ስለ ማመፃቸው በማስታወስ መልስ ሰጠ። ከዚያም እንዲህ አለ፣ “እናንተ አንገተ ደንዳኖችና ዓመፀኞች ሕዝብ ልክ ቅድማያቶቻችሁ እግዚአብሔርን እንደ ተቃወሙትና ነቢያቱን እንደ ገደሉ ሁልጊዜ መንፈስ ቅዱስን ትቃወማላችሁ። እናንተ ግን ከእነርሱ ይልቅ የባሰ ነገር አድርጋችኋል። መሲሑን ገድላችኋል!”
የሃይማኖት መሪዎቹ ይህንን በሰሙ ጊዜ፣ ጆሮአቸውን እስኪደፍኑና ከፍ ባለ ድምፅ እስኪጮኹ ድረስ በጣም ተቈጡ። እስጢፋኖስን ከከተማይቱ ውጪ ጐተቱትና ሊገድሉት በድንጋይ ወገሩት።
እስጢፋኖስ በመሞት ላይ እያለ፣ “ኢየሱስ ሆይ፣ ነፍሴን ተቀበላት” ብሎ ጮኸ። ከዚያም በጉልበቱ ተንበረከከና፣ “ጌታ ሆይ፣ ይህንን ኃጢአት አትቊጠርባቸው” ብሎ እንደ ገና ጮኸ። ከዚያ በኋላ ሞተ።
ሳውል የተባለ ወጣት እስጢፋኖስን ከገደሉት ሰዎች ጋር ተስማማና በእርሱ ላይ ድንጋይ በሚወረውሩበት ጊዜ ልብሳቸውን ይጠብቅ ነበር። በዚያን ዕለት በኢየሩሳሌም የነበሩ ብዙ ሰዎች የኢየሱስን ተከታዮች ማሳደድ ጀመሩ፣ ስለዚህ አማኞቹ ወደ ሌሎች ስፍራዎች ሸሹ። ነገር ግን ስደቱ ቢኖርም እንኳ፣ በሄዱበት ስፍራ ሁሉ ስለ ኢየሱስ ሰበኩ።
ፊልጶስ የተባለ የኢየሱስ ደቀ መዝሙር በስደቱ ጊዜ ከኢየሩሳሌም ከሸሹት አማኞች አንዱ ነበር። ወደ ሰማርያ ሄዶ ስለ ኢየሱስ ሰበከና ብዙ ሰዎች ዳኑ። ከዚያ በኋላ አንድ ቀን ከእግዚአብሔር የተላከ መልአክ በምድረ በዳ ወዳለ አንድ መንገድ እንዲሄድ ለፊልጶስ ነገረው። ፊልጶስ በመንገዱ በመሄድ ላይ እያለ አንድ ታዋቂ ኢትዮጵያዊ ባለ ሥልጣን በሰረገላው ሲሄድ ዐየ። ወደዚህ ሰው ሄዶ እንዲያነጋግረው መንፈስ ቅዱስ ለፊልጶስ ነገረው።
ፊልጶስ ወደ ሰረገለው በቀረበ ጊዜ፣ ኢትዮጵያዊው ነቢዩ ኢሳይያስ ከጻፈው ውስጥ አንዱን ክፍል ሲያነብ ሰማ። ሰውዬው እንዲህ አነበበ፣ “እንደሚታረድ በግ ነዱት፣ በግ ዝም እንደሚል አንድም ቃል አልተናገረም። በፍርድ ተወሰደ፣ አላከበሩትምም። ከሕያዋን ምድር አስወገዱት።”
ፊልጶስ ኢትዮጵያዊውን፣ “የምታነበውን ታስተውለዋለህን?” ብሎ ጠየቀው። ኢትዮጵያዊው፣ “አይደለም። የሚያስረዳኝ ሰው ሳይኖር ላስተውለው አልችልም። እባክህን ናና ከጐኔ ተቀመጥ። ኢሳይያስ የጻፈው ስለ ራሱ ነውን ወይስ ስለ ሌላ ሰው?”
ኢሳይያስ የጻፈው ስለ ኢየሱስ መሆኑን ፊልጶስ ለኢትዮጵያዊው አብራራለት። ደግሞም ፊልጶስ ስለ ኢየሱስ የሚናገረውን የምሥራች ሊነግረው ሌሎች የእግዚአብሔር ቃል ክፍሎችን ተጠቀመ።
ፊልጶስና ኢትዮጵያዊው እንደ ተጓዙ፣ ውሃ ወዳለበት ስፍራ ደረሱ። ኢትዮጵያዊው፣ “እነሆ፣ በዚያ ቦታ ውሃ አለ! ልጠመቅን? አለ። ለነጂውም ሰረገላውን እንዲያቆመው ነገረው።
ስለዚህ ወደ ውሃው ወረዱ፣ ፊልጶስም ኢትዮጵያዊውን አጠመቀው። ከውሃው ከወጡ በኋላ መንፈስ ቅደስ በድንገት ፊልጶስን ወደ ሌላ ስፍራ ነጠቀው፤ ስለ ኢየሱስ ለሰዎች መናገሩንም ቀጠለ።
ኢትዮጵያዊው ኢየሱስን በማወቁ እየተደሰተ ወደ አገሩ ለመመለስ ጕዞውን ቀጠለ።